ድርቡ የጤና ዘርፍ ችግር በአፄ ምኒልክ ዘመን በነጮች የተዋወቀው የዘመናዊ ሕክምና ጥበብ ጥሩ መሠረት ጥሎ አልፏል፡፡ ነገር ግን ለነጮች ብቻ የተሰጠ የማዳን ፀጋ እስኪመስል አንድም ኢትዮጵያዊ ሳይንሱን ሳይጋራ ብዙ ቆይቶ ነበር፡፡ በዚህ መካከል ነው ለአገሪቱ የመጀመርያው ጥቁር ዶክተር ሐኪም ወርቅነህ እሸቱ ለነጮች ብቻ ተብሎ ወደተተወው የሥራ መደብ የገቡት፡፡ አጋጣሚው በአገሬው ዘንድ ግርምትን ያጫረና ኢትዮጵያዊም ተምሮ ወገኖቹን ማከም እንደሚችል አዲስ ተስፋ የፈነጠቀ ነበር፡፡ ሐኪም ወርቅነህ የሕክምና ትምህርት መማር የቻሉት ባልታሰበ አጋጣሚ ነበር፡፡ ትውልዳቸው ጎንደር ነው፡፡ ቤተሰቦቻቸው ከጎንደር ወደ መቅደላ በግዞት የተወሰዱት በአፄ ቴዎድሮስ ዘመነ መንግሥት ነበር፡፡ ብዙም ሳይቆይ ከብሪታንያ መንግሥት ጋር በተፈጠረው ግጭት መቅደላ የጦር አምባ ሆነች፡፡ አፄውም የገዛ ጥይታቸውን ጠጥተው እስከ መጨረሻው አንቀላፉ፡፡ የእንግሊዝ ወታደሮችም የአባቱ አስከሬን ላይ ተደፍቶ ሲያለቅስ ያገኙትን ሕፃን ዓለማየሁ ቴዎድሮስንና የጠፉበትን ወላጆቹን ፍለጋ ሲማስን የነበረውን ወርቅነህን ወሰዷቸው፡፡ ክስተቱ በአገሪቱ ታሪክና የጦር ውሎ ትልቅ ቦታ የሚሰጠውና ገናናውን ንጉሥ ያሳጣ ቢሆንም፣ በተቃራኒው ለትንሹ ልጅ ለወርቅነህ ጥሩ አጋጣሚን የፈጠረ ነበር፡፡ የቀዶ ጥገና ሕክምና መማር የቻሉት ከአገር ስለወጡ ነበር፡፡ ሌሎች የተለያዩ የሕክምና ትምህርቶችንም መከታተል ችለዋል፡፡ በህንድ በበርማ በተለያዩ የሕክምና ኃላፊነቶች ሠርተዋል፡፡ ወደ ኢትዮጵያ የተመለሱት እ.ኤ.አ. በ1890ዎቹ ነበር፡፡ ኢትዮጵያዊውን ዶክተር ማየት ለብዙዎች ትንግርት ነበር፡፡ የዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታል ሜዲካል ዳይሬክተር ሆነው አገልግለዋል፡፡ የምኒልክም የቅርብ ሐኪም ሆነው ሠርተዋል፡፡ ወገኖቻቸውን በሕክምና ጥበብ ፈውሰዋል፡፡ እሳቸውም በበኩላቸው ሦስት ወጣቶች ከኢትዮጵያ መጥተው ሕክምና እንዲያጠኑ አድርገዋል፡፡ በዚህ የተጀመረው የኢትዮጵያ ዘመናዊ የሕክምና ሳይንስ ዛሬ ላለበት ደረጃ ለመብቃት ብዙ ውጣ ውረዶች አሳልፏል፡፡ ከምዕት ዓመት በፊት አንድ ሐኪም ብርቅ የሆነባት ኢትዮጵያ አሁን በሺዎች የሚቆጠሩ ሐኪሞችን አፍርታለች፡፡ እ.ኤ.ኤ. ከ2009 እስከ 2015 ባሉት ዓመታት የሕክምና ትምህርት የሚሰጥባቸው ተቋማት ቁጥር ወደ 35 ማደጉን፣ ከእነዚህ ኮሌጆች መካከል 28ቱ የመንግሥት፣ ሰባቱ ደግሞ የግል መሆናቸውን፣ በየዓመቱ ወደ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በመግባት ሕክምና የሚያጠኑ ተማሪዎች ቁጥርም ከ20 ወደ 4,000 ማደጉን፣ የሐኪሞች ቁጥርም ከ1,540 ወደ 5,372 ከፍ ማለቱን ዓምና የወጣው የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የሰው ኃይል ልማት ስትራቴጂ ያሳያል፡፡ አጠቃላይ የሕክምና ባለሙያዎች ከሕዝቡ ያላቸው ንፅፅርም ከነበረበት 0.84 ባለሙያ ለ1,000 ወደ 1.5 ለ1,000 መሆን ችሏል፡፡ ይህም የተመዘገበው ባለፉት አምስት ዓመታት ነው፡፡ በእነዚህ ዓመታት በሕክምናው ዘርፍ ካለፉት ጊዜያት በተሻለ የተወሰኑ ርቀቶችን መሄድ ተችሏል፡፡ ካለው የበሽታዎች ተለዋዋጭነትና የሕዝብ ቁጥር ዕድገት አንፃር ሲታይ ግን ለውጡ እምብዛም ነው፡፡ ለከባድ ሕክምና ከፍተኛ ወጪ አውጥተው ባህር ማዶ የሚሄዱ፣ ተገቢውን ሕክምና ሳያገኙ ሕይወታቸው የሚያልፍ ዜጎች ቁጥር አሁንም ከፍተኛ ነው፡፡ የዘመናዊ ሕክምና ቴክኖሎጂዎች እጥረት በዚህ ላይ የሚኖረው ሚና ትልቅ ቢሆንም፣ የባለሙያዎች ቁጥር ከሕዝቡ ቁጥር አንፃር አነስተኛ መሆንም ሌላው ምክንያት ነው፡፡ በተለይም በልዩ ልዩ የሕክምና ዓይነቶች ስፔሻላይዝና ሰብ ስፔሻላይዝ ያደረጉ ባለሙያዎች በጣም አነስተኛ ናቸው፡፡ ለዚህም በየሕክምና ተቋማቱ፣ ‹‹ስፔሻሊስቱ እስኪመጣ›› ብለው ለሰዓታት የሚጠባበቁ ታካሚዎችና አስታማሚዎች ምስክር ናቸው፡፡ ከስንት አንድ በሆኑት ስፔሻሊስቶች ለመታከም ዕድለኛ መሆንም ይጠይቃል፡፡ ‹‹ካለው የበሽታ ተለዋጭነት አንፃር ስፔሻሊስቶች በደንብ ያስፈልጉናል፡፡ ከዚህ አንፃር ሲታይ ያሉት ስፔሻሊስቶች ቁጥር በጣም ዝቅተኛ ነው፡፡ የተቀመጠውን ዓለም አቀፍ ስታንዳርድ ለመድረስም ብዙ መሥራት ይጠይቃል፤›› ያሉት በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የፕሪሰርቪስ ኤጁኬሽን ቲም ሊደሩ አቶ አሰግድ ሣሙኤል ናቸው፡፡ በየጤና ተቋማቱ ያሉ ስፔሻሊስቶች ከሁለትና ሦስት የማይበልጡና እንደ ብርቅ የሚታዩ መሆናቸውን በመግለጽም በዚህ ረገድ ብዙ ወደኋላ መቅረቱን ያክላሉ፡፡ ሲንቀሳቀሱም በኢንተርኖች ተከበው አሊያም ልጄን ከሞት አፋፍ መልስልኝ የሚልና ሌላም የሞትና የሕይወት ጉዳይ ይዘው በሚማፀኗቸው አስታማሚዎች ተከበው ነው፡፡ ‹‹ስፔሻሊስቱ አልገባም›› ተብለው በቀጠሮ የሚመላለሱ ተመላላሽ ታካሚዎችም ጥቂት አይደሉም፡፡ በሆነ ሕክምና ስፔሻላይዝ ያደረገ ባለሙያ የቀጠሩ የግል የሕክምና ተቋማትም በየማስታወቂያው ስፔሻሊስቱ ስለሚሠራው ተዓምር ማስነገር ሥራቸው ሆኗል፡፡ ማሻሻጫ የማድረግ ያህል ስሙን ይጠቀሙታል፣ ይኩራሩበታልም፡፡ ስፔሻሊስቶች በሌሎች ሐኪሞች ዘንድም ክብር ይቸራቸዋል፡፡ አልፎ አልፎ ጣል የሚደረጉ ቅመሞች ናቸውና ይህም ሲያንሳቸው ይሆናል፡፡ በየጤና ተቋማቱ ካለው ነባራዊ ሁኔታ አንፃር ሲታይ ብዙ ስፔሻላይዝ ያደረጉ ሐኪሞች በየሆስፒታሉ እንደማይገኙ የሚናገሩት የዘውዲቱ መታሠቢያ ሆስፒታል ሜዲካል ዳይሬክተር ዶክተር የኔዓለም አየለ ናቸው፡፡ እንደ እሳቸው ገለጻ፣ በሆስፒታሉ 22 ስፔሻሊስቶች ይገኛሉ፡፡ ስፔሻሊስቶቹም የጋይናኮሎጂ፣ የቀዶ ሕክምና፣ የውስጥ ደዌ፣ የቆዳ፣ የአዕምሮ፣ የነርቭ፣ የሕፃናት ሕክምና ባለሙያዎች ሲሆኑ፣ የሕፃናት ሕክምና ላይ የሚሠሩ የሰብ ስፔሻሊቲ ሕክምና ባለሙያዎችም አሉ፡፡ እንደዚህም ሆኖ ዜጎች የሚፈልጉትን ሕክምና ለመስጠት በቂ እንዳልሆኑ ይናገራሉ፡፡ በአገሪቱ ከሚገኙ የተሻለ የስፔሻሊስት ሐኪሞች ስብጥር ካላቸው ጥቂት ተቋማት መካከል የሆነው ሆስፒታሉ ሌሎች የስፔሻሊስትና ሰብ ስፔሻሊስት ሐኪሞች ግን የሉትም፡፡ በጋስትሮኢንትሮሎጂ፣ ካርዲዮሎጂ፣ ኢንዶክሮሎጂ የሕክምና ዘርፍ ባለሙያ የለውም፡፡ ‹‹በእነዚህ ዙሪያ በአጠቃላይ በአገሪቱ ችግር አለ፤›› የሚሉት ዶክተር የኔዓለም፣ በሰብ ስፔሻሊቲ በሚሠሩ ሕክምናዎች ረገድ የነርቭና የጨቅላ ሕፃናት ሐኪሞች ብቻ እንዳሉ ይናገራሉ፡፡ በእነዚህ የሕክምና ዘርፎች በሠለጠኑ ባለሙያዎች መታየት ያለባቸው ታካሚዎች ሲያጋጥሙም ከቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ባለሙያ በመዋስ አሊያም ተካሚዎቹን ወደ ተቋሙ በመላክ አስፈላጊውን ሕክምና እንዲያገኙ እንደሚደረግ ይናገራሉ፡፡ ከፍተኛ የባለሙያዎች እጥረት ካለባቸው የሕክምና ዘርፎች አንዱ ሰብ ስፔሻሊቲ ጋስትሮኢንትሮሎጂ የሕክምና ዘርፍ ነው፡፡ ጋስትሮኢንትሮሎጂ የምግብ መውረጃ ጉሮሮ፣ ጨጓራ፣ አንጀት፣ ቆሽት፣ ጉበት፣ የሐሞት ከረጢትና የሐሞት መስመሮችን የሚያጠቃልል የሕክምና የሳይንስ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ጋስትሮኢንትሮሎጂ ማኅበር ፕሬዚዳንት ዶክተር ብርሃኔ ረዳኢ እንደሚሉት፣ የጋስትሮኢንትሮሎጂ ሕክምና ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ተፈላጊነቱ እየጨመረ ይገኛል፡፡ ለዚህም ዋነኛው ምክንያት በተጠቀሱት የአካል ክፍሎች ላይ የሚከሰቱ በሽታዎች ሥርጭት በከፍተኛ መጠን እየጨመረ መምጣቱ ነው፡፡ ከእነዚህ ሕመሞች አንደኛው የጉሮሮ ካንሰር ነው፡፡ ሕመሙ ጉሮሮን በማጥበብ ሕመምተኛው ምግብ እንዳይውጥ ያግዳል፡፡ በሽታው በሰዎች ላይ ከሚፈጥረው ስቃይ በተጨማሪ ምግብ እንዳይመገቡ የሚያግድበት ሁኔታ፣ ታማሚዎችን ይበልጥ እንዲዳከሙ እንደሚያደርግ ዶክተሩ ይናገራሉ፡፡ ‹‹ጨጓራ አለብኝ የማይል የለም፤›› የሚሉት ዶክተር ብርሃኔ፣ በጨጓራ መቆጣት፣ መላጥ፣ መቁሰል፣ መድማት ካንሰር በመሳሰሉት የጨጓራ ሕመሞች የሚሰቃዩ በርካቶች መሆናቸውን ይናገራሉ፡፡ የአንጀት መቁሰል የአንጀት ካንሰር፣ ሄፒታይተስ የመሳለሱትም ብዙዎችን ለስቃይ እየዳረጉ የሚገኙ በሽታዎች ናቸው፡፡ ‹‹በአጠቃላይ ሁሉም ላይ ትልቅ ችግር አለ፡፡ በሽታዎቹን ሊያክሙ የሚችሉ ባለሙያዎችን ማግኘት ከባድ ነው፤›› በማለት ከጊዜ ወደ ጊዜ ሥርጭቱን እያሰፋ ከሚገኘው የበሽታው ዓይነት በተጨማሪ ሕክምናውን መስጠት የሚችሉ ሰዎች በጣት የሚቆጠሩ መሆናቸው ድርብ ችግር እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ ሕክምናው የሚሰጠው በሰብ ስፔሻሊስት ባለሙያዎች መሆኑ ደግሞ የባለሙያዎቹን ተደራሽነት ይበልጥ እንዲሳሳ አድርጎታል፡፡ ትምህርቱ የሚሰጠው በጥቁር አንበሳና በጳውሎስ የሕክምና ኮሌጆች ሲሆን፣ በዓመት የሚመረቁት ተማሪዎች ከሦስት እንደማይበልጡ ይናገራሉ፡፡ የእነዚህ ባለሙያዎች ቁጥር ከሌላው በተለየ እጅግ ውስን የሆነው ትምህርቱን ጨርሶ ወደ ሥራ ለመግባት የሚወስደው ጊዜ ረዥም በመሆኑ እንደሆነ ዶክተር የኔ ዓለም ይናገራሉ፡፡ እሳቸው እንደሚሉት፣ የስፔሻሊቲ ሕክምና ትምህርት ለመጨረስ በትንሹ ሦስት ዓመታት ይፈጃል፡፡ በሰብ ስፔሻሊቲ ለመቀጠል ደግሞ ተጨማሪ ሁለት ዓመታት በትምህርት ላይ መቆየት ግድ ይላል፡፡ በእነዚህ በተሰጡት ዓመታት ተምረው የሚጨርሱ ጥቂቶች ናቸው፡፡ አብዛኛዎቹ በተለያዩ አጋጣሚዎች ትምህርቱን ያቋርጣሉ፡፡ ‹‹ችግሩ በወራት ዕድሜ ባይሆንም በቅርብ ዓመታት ውስጥ የሚፈታ ነው፤›› በማለት ችግሩን ለመቅረፍ የተጀመሩ ሥራዎች መኖራቸውን ይገልጻሉ፡፡ ዘውዲቱ መታሠቢያ ሆስፒታል በበኩሉ 35 የስፔሻሊቲ ሕክምና ተማሪዎችን ለማስተማር እንቅስቃሴ ጀምሯል፡፡ ትምህርቱን ለመስጠት የሚያስፈልገውን ዕርምጃ አንድ ብሎ ለመነሳትም ለተመረጡ ባለሙያዎች ፈተና ለመስጠት ተዘጋጅቷል፡፡ ‹‹ፈተናውን ካለፉ ሁሉንም እናስተምራለን፤›› ሲሉ ችግሩን ለመቅረፍ አንድ ዕርምጃ የሆነውን ጅምር ይገልጻሉ፡፡ በፕላኑ መሠረት እ.ኤ.ኤ. በ2016 በጤና ተቋማት የሚሠራጨው አጠቃላይ የሰው ኃይል 219,542 ሲሆን፣ ከእነዚህ መካከል 150,534 በልዩ ልዩ የሕክምና ሳይንስ የሚሠሩ ባለሙያዎች ናቸው፡፡ እ.ኤ.አ. በ2020 የሐኪሞችን ቁጥር ወደ 9,836, በ2025 ደግሞ ወደ 15,676 ለማሳደግ ዕቅድ ተይዟል፡፡ የጤና ተቋማትን በማስፋፋት ረገድም እንደዚሁ እየተሠራ ይገኛል፡፡ ከአሥር ዓመታት በፊት በአገሪቱ የነበሩ የጤና ተቋማት ቁጥር 279 ነበር፡፡ በአሁኑ ወቅት ግን 4,000 ደርሰዋል፡፡ 87 ብቻ የነበረው የሆስፒታሎች ቁጥርም ወደ 411 ከፍ ብሏል፡፡ የስፔሻሊቲ ሕክምና ላይ የሚሠሩ ሐኪሞች ቁጥር እጅግ ውስን መሆኑ ግን ብዙም መለወጥ ያልተቻለ አንዱ የአገሪቱ ሕክምና ዘርፍ ድክመት ሆኖ ቀጥሏል፡፡ በየጤና ተቋማት ያለው የባለሙያ እጥረት እንደ ሙያው የተለያየ ነው፡፡ ከፍተኛ እጥረት ከሚታይባቸው የሙያ ዓይነቶች መካከልም የፋርማሲ ባለሙያዎች፣ ሜዲካል ላቦራቶሪ ባለሙያ፣ የሰመመን ስፔሻል ሐኪሞች መሆናቸውን በቅርቡ በተካሄደ አንድ የጤና ኮንፈረንስ ላይ የጤና ጥበቃ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ከበደ ወርቁ ገልጸዋል፡፡ የስፔሻሊቲ ሐኪሞችን ቁጥር በየዓመቱ ከእጥፍ በላይ ለመጨመር እንዲሁም በስምንት ዓመታት ውስጥ ወደ 10,000 ለማድረስ ዕቅድ ተይዟል፡፡ በአሁኑ ወቅት በሥራ ላይ የሚገኙት ስፔሻል ሐኪሞች 1,500 እንኳን እንደማይሞሉ ዶክተር ከበደ ተናግረዋል፡፡ ቁጥራቸውን ለመጨመር እንዲቻልም በአገሪቱ ከሚገኙ የመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች ምክክር መደረጉንም አብራርተዋል፡፡ እስካሁን ለነበረው የስፔሻሊቲና ሰብ ስፔሻሊቲ ሐኪሞች እጥረት በምክንያት ከሚነሱ ነገሮች አንዱ ‹‹ተቋማት መቀበል በሚችሉበት አቅም እየተቀበሉ አልነበረም፡፡ ጉዳዩ ላይ ትኩረት አድርጎ የመሥራት ችግር አለ፤›› በማለት አቶ አሰግድ ይገልጻሉ፡፡ ስፔሻሊቲ ሐኪሞች ከጠቅላላ ሆስፒታል ጀምሮ ወደ ላይ ለሚገኙ የጤና ተቋማት የሚመደቡ ሲሆን፣ በየዓመቱ 1,000 ስፔሻሊስቶችን ለማስመረቅ ዘመቻ መጀመሩን፣ ለዚህም 12 ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት መለየታቸውን አቶ አሰግድ ይናገራሉ፡፡ ይህ ከወረቀት ባለፈ ምን ያህል ተፈጻሚ ይሆናል የሚለው ነገር አጠያያቂ ቢሆንም፣ ለመቶ ዕርምጃ መነሻው አንድ ነውና ሌላው ቢቀር በጉዳዩ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ በመሰራቱ ብቻ ለዓመት 1,000 ባይሆን 100 ስፔሻሊስቶችን ማብቃት ትልቅ ነገር ነውና ይበል የሚያሰኝ ነው፡፡ 1 October 2017 ሻሂዳ ሁሴን Repoter News Reporter